Sunday, November 7, 2021

ኢትዮጵያ ኢጣሊያን አድዋ ላይ እንዴት አሸነፈች? ወታደራዊ ስትራቴጂ











































































ኢትዮጵያ ኢጣሊያን አድዋ ላይ እንዴት አሸነፈች? ወታደራዊ ስትራቴጂ

የጦርነት ታሪክ ፀሐፍት በአንድ ነገር ይስማማሉ። አንዲት ሀገር በጦር ሜዳ አሸናፊ የምትሆነው በፍትሃዊ ጦርነት ውስጥ ተሳታፊ ከሆነች ብቻ ነው። ጦርነቱ ፍትሃዊ ካልሆነ ግን መቼም ቢሆን አሸናፊ አትሆንም። ይህን እሳቤ ይዘን ወደ አድዋ ጦርነት ገፊ ምክንያቶች ስናመራ ኢትዮጵያ በዚያ ዘመን የገባችበት ጦርነት ፍትሃዊ ሆኖ እናገኘዋለን።

ለምን? የአድዋ ጦርነት መነሻ ዋና ምክንያት የውሃ ዲፕሎማሲ ነው። እንግሊዝ ምስራቅ አፍሪካን በተለይም የዓባይ ወንዝ ተፋሰስን ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር ካላት ፍላጎት የመነጨ በመሆኑ። በ19ኛው ክፍለ ዘመን በተደረገው የቅኝ ግዛት መስፋፋት እንግሊዝ፣ፈረንሳይ ፣ ቤልጂየም እና ኢጣሊያ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል። በእርግጥ የኢጣሊያ አመጣጥ የሀገር ውስጥ ፖለቲካዊ ገና የውህደት ዑደቱን ባለማጠናቀቁ ዘግየት ብላ ነው የተቀላቀለችው።

እንግሊዞች እና ግብፆች በሱዳኖች የደረሰባቸውን ከበባ ለመቋቋም ከኢትዮጵያዊው ንጉሠ ነገሥት አፄ ዮሐንስ ጋር ተፈራረሙ፤ የሒዎቴ ወይም የአድዋ ስምምነትን። በሱዳን ከበባ የፈተፀመባቸው የግብፅ እና የእንግሊዝ ወታደሮች በኢትዮጵያ በኩል አድርገው በሰላም መውጣት እንዲችሉ ማድረግን ታሳቢ በማድረግ። በዚህ ስምምነት እንግሊዝ ለኢትዮጵያ ወደቦችን ክፍት ለማድረግ ተስማምታለች።ምስራቅ አካባቢ ግብፅ ተቆጣጥራው የነበረውን ወደብም ለቃ ለመውጣት እንዲሁ።

እንግሊዝ ግን ለኢትዮጵያ የገባችውን ቃል አጥፋ በተቃራኒው ምስራቅ አፍሪካ ውስጥ ተገዳዳሪ ሆና የመጣችባትን ፈረንሳይን ለመግታት ኢጣሊያን ጋበዘቻት። ኢጣሊያን በእንግሊዝ ግብዣ የምገባባት የወዲያው ምክንያት ፈረንሳይን መግታት የሚል ቢሆንም የሮም ቄሳር ኃይላት ግን የራሳቸውን ቀመር በአባከሳዊ ስሌት እያሰሉ ነበር። በእንግሊዝ ጋባዥነት ወደ ኢትዮጵያ ሰሜናዊ ግዛት የገባችው ኢጣሊያ ከአፄ ምኒልክ ጋር በውጫሌ ስምምነት ፈረመች።

ያ ስምምነት ግን በመርዝ የተለወሰ ሀረግ እና አንቀጾችን ይዞ ነበር። አንቀፅ 17 የኢጣሊያንኛ ቋንቋ ይዘቱ ፍፁም የተለየ ነበር። ኢትዮጵያን በተዘዋዋሪ የኢጣሊያ የቅኝ ተገዥ ያደረገ ፍሬ ሀሳብ የያዘ ነበር። ኢትዮጵያ ነገሩን ውድቅ አደረገች ። አሁን ሁሉ ነገር ወደ ጦር አውድማ እየዞረ ነው። የቄሳር ኃይላት በዚያ ታላቂቱን ሀገር በቅኝ ግዛት መዳፋቸው ለማስገባት ከቋመጡ ከራርመዋል። ታላቁ አርበኛ ራስ አሉላ አባ ነጋ በዶጋሊ ያደረሰባቸውን ከባድ ኪሳራ እና ውርደት ለመበቀል አሰፍስፈው ተሰልፈዋል።

ታላቂቷ አፍሪካዊት ሀገር የምስራቅ አፍሪቃዋ ኮከብ ደግሞ በታላቁ ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒልክ በኩል አዋጭ ያለችውን ዝግጅት ለአይቀሬው ጦርነት እያዘጋጀች ነው። ሃገራዊ ዝግጅቱ በንጉሠ ነገሥቱ በአፄ ምኒልክ የዘመቻና የጦርነት አዋጅ ይጀምራል።የአዋጁ ይዘት የዘመቻ ጥሪን ለኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ነዋሪዎችና ለሹማምንቶች ኢትዮጵያ በጠላት ጥርስ ውስጥ መግባቷንና የቅኝ ተገዥነት ዕጣፋንታዋ መቃረቡን፣በሕዝቦች የተባበረ ክንድ ግን ጠላትን መመከት እና በቅኝ መገዛት እንደማይቻል የተገነዘቡት ንጉሠ ነገሥት ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝቦች ይህን ታላቅ የጦር ክተት አዋጅ አወጁ።

ከታሪክ መረጃ ምንጮች የምንገነዘበው የምንረዳውም የሩቁንም ሆነ የቅርቡን የዘማች ሠራዊት ኃይል በማደረጃት ከሸዋና ከአካባቢው የተነሳው ዘማች ኃይል ወሎ ወረ ኢሉ ላይ እንዲከት፣ ከጎጃም፣ ከደምቢያ፣ ከቋራ፣ ከበጌምድር እና ከጨጨሆ በላይ ያለውን ሃገር ሁሉ አሸንጌ ላይ እንዲከት፣ የሰሜኑንና የወልቃይት ጠገዴንም ሰው መቀሌ ላይ እንዲከት፣ የሐረር ዘማች በአዲስ አበባ በኩል ገና የጥቅምቱ ዘመቻ ሳይጀምር አዲስ አበባ ገብቶ ወረ ኢሉ እንዲከት፣ የወለጋው ሠራዊት መግባት የቻለው ገብቶ በክረምቱ በመስከረም ስለሚበረታ በውሃ ሙላት እንዲቆይ ተደርጓል።

ዋናው ቁም ነገር ግን አዋጁ ሃገራዊ ንቅናቄን መፍጠሩና መተግበሩ ስለነበር በትክክል ተተግብሯል ለማለት ይቻላል። ታላቁ ንጉሠ ነገሥት ሐይማኖትህን እና ሚስትህን የሚሉ ግዝፈት የሚነሱ ጉዳዮችን ማካተታቸውን ስንመረምር ምን ያህል አርቆ አሳቢ መሆናቸውን እንረዳለን። ሰው በሚስቱ እና በሃይማኖቱ ከመጡበት ቀናኢ ነውና !

የዘመተው ሠራዊት ፍጹም ሕብረብሔራዊ ነበር። እገሌ እና እገሌ ሳይባባሉ ፈቃደኝነት ላይ በተመሠረተ የንጉሠ ነገሥቱን አዋጅ ተቀብለው በሃገራዊ፣ በወገናዊና በባሕላዊ ጉዳዮች የጋራ ትሥሥር፣ የጋራ መግባባትና በኢትዮጵያዊነት ወኔ ተሞልተው ታሪክ ለመሥራት የተሠባሰቡ ዜጎች እንጂ ግዴታ፣ ኃይልና በወቅቱ ሕግ አስገዳጅነት የዘመቱ አልነበሩም።

ኢትዮጵያዊ ማንነታቸውንና የሃገራቸውን የነፃነትና የሉዓላዊነት ጉዳይ ላይ ያተኮሩ እንጂ በትናንሽ ቁርሾዎች ልዩነት ፈጥረው ከዋናው ሃገር የመጠበቅ ተልዕኮ ያፈነገጡም አልነበሩም። በዘመቻው ሂደት የታየው የጋራ ክተት ጥሪ፣የታየው የጋራ ዓላማ ፅናት የተሞላበት ረዥሙ የዘመቻ ጉዞ፣ ሣይቸኩሉ ሁሉንም በልባቸው አድርገው የጋራ ድል ማስመዝገቡ የዚያ የአድዋ ዘመቻ የጦር አመራር የጥበብ የምክክር ብስለትና ብቃት ነበር። ይህ ባይሆን ኖሮ የዓድዋን ድል ማስመዝገቡ አስችጋሪ በሆነ ነበር።

 

የዘመቻ ስንቅ ሁኔታ

ከንጉሠ ነገሥቱ ወረገኑ፣ ከእቴጌይቱ ወረገኑ፣በግብር መልክ እንዲገባ በየደረሱበት አካባቢ ከተሰበሰበው የተለያየ የአቅርቦት አይነት ሌላ፣ ዋናው የስንቅ የጀርባ አጥንት ሆኖ ጦርነቱን በብቃት ለማሸነፍ የተቻለው ከዘመቻ ጉዞ ደርሦ መልስን በማካተት በተጨማሪም በውጊያዎችም ወቅቶችም ቢሆን የሕዝቦችን አስተዋፅኦ ይህ ነበር ብሎ መገመቱ ይከብዳል። በተለይ የትግራይ የጦር አውድማዎች አካባቢዎች የነዋሪዎችን ያላሰለሰ ድጋፍ መገመቱ አይከብድም። ወደርየለሽ የአቅርቦት መረባረብ ተደርጓል (ገብረ ሥላሴ ገፅ 227 _268)።

 

በአድዋ ጦርነት የተሰለፈው ዘመቻ ሠራዊ የጦር ኃይሉና መሣሪያ አቅም

ከኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ ሕዝቦች ተዋፅኦ የነበረ ሲሆን፣ እንደ ዘመኑ አሠራር በተዋረድ የዘመቻ ጥሪ ደርሷቸው የዘመቱ ነበሩ። ባሳለፉበት የውጊያ አውድማዎችና በተሳተፉበት የዓድዋ ግንባር ላይ በታሪክ ውስጥ ሊደመሠሥ የማይቻለውን የዓለም፣ የአፍሪቃ እና የኢትዮጵያን ጥቁር ህዝቦች ድል እውን እንዲሆን አድርገዋል። የተለያዩ የዚያ ሠራዊት አመራርና አባላት በተለያዩ የጦር ሜዳዎች ውስጥ ወርቅ በእሳት ግሎ እንደሚፈተን በጦርነት የተፈተኑና የጦርነትን ምንነት አብጠርጥረው የሚያውቁ ነበሩ። በኢትዮጵያ ይሁን በኢጣሊያኑ ወገን የተለያዩ ካሊበር አቅም የነበራቸው መድፎች፣መትረየሶችና ሌሎች ነፍስ ወከፍ መሣሪያዎችን በሥራ ላይ ውለዋል።

የኢትዮጵያው ዘማች ሠራዊት የተወሰኑ ከባድ መሣሪያዎች ነበሯቸው። የመሣሪያዎችን ዝርዝርና አቅማቸውን፣ እንዲሁም በሁለቱም ጎን የነበረውን የጦር ኃይሉን አቅም በደንብ ማየት ይቻላል። የኢጣሊያኑ ተዋጊ 56 መድፎችን አሰልፏል። (በርክሌ) ሁለት የኢጣሊያን ባትሪዎች ከባድና ፈጣን ተወንጫፊዎችን እንደተጠቀሙ ዕይታውን ፅፏል። ኢትዮጵያውያን በዓድዋ ላይ ያሰለፉት 42 መድፎች ነበሯቸው። የወቅቱ ወታደራዊ ጠበብቶች ግን ለዓድዋው ድል ዋነኛ ምክንያት የከባድ መሣሪያው መታጠቅ አልነበረም። የደነደነው ኢትዮጵያዊ የጀግኖች ወኔ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዘማች ሠራዊት መድፎች ከተለያዩ ምንጮች የተገኙ ነበሩ። በግዥ፣ በስጦታ፣ አፄ ዮሐንስ ከጉንዳት ና ከጉራዕ ጦርነት ወቅት ከግብፆች የማረኳቸው መትረየሶችና ሌሎች ጠመንጃዎች ሁሉ ተደራጅተው ለውጊያ አገልግሎት ውለዋል። ዋናው ቁም ነገር ኢትዮጵያ የአውሮፓ ሠራሽ ከባድ መሣሪያዎችን ዓድዋ ጦርነት ላይ መጠቀሟን መገንዘብ ነው!!

የኢትዮጵያዊያኑ የመድፍና የማሽን ጦር መሣሪያዎች በብቃት የመጠቀሙ ሁኔታ በወቅቱ ወታደራዊ ጠበብቶች ተገምግመው፣ የግምገማው ውጤት ሲገለፅ የአድዋ ውጊያዎች የአፍሪቃ ኃይል የሆነው የኢትዮጵያ ዘማች ሠራዊት በቅኝ ገዥዎች ሠራሽ መሣሪያዎች ቀኝ ገዥውን ኢጣሊያንን አንበረከከ እንጂ የቅኝ ግዛት ናፋቂዋ ኢጣሊያ በቅኝ ገዥዎች ሠራሽም ይሁን በራሷ በሠራችው መሣሪያ ባለውጤት እንዳልነበረች የዓድዋ ተራሮች ገሃድ አድርገውታል።

በኢትዮጵያ በኩል በፈረንሣይ ገበያዎች በኩል የገቡትን ከባድ መሣሪያዎችን መጠቀም መቻሉን ገልፀዋል። የኢትዮጵያ ተዋጊዎች መሣሪያዎች የኢጣሊያን ኃይል ፀጥ ማሠኘታቸው የኢጣሊያኑ ኃይል ከአላጄና ከመቀሌ የወጊያዎች ሽንፈትና ውድቀት ያለመማራቸውን የሚያረጋግጥ ነበር። በኢትዮጵያ በኩል ከዘመናዊ ጦር መሣሪያዎች በተጨማሪ ጦርነቱ እየተጋጋለ ሲሄድ ጎራዴና በለበን ነፍስ ወከፍ ጠመንጃዎችን በመጠቀም ያደረጉት ወሳኝ ውጊያ የአድዋን ጦርነት ድል እንዲያጠናቅቁ ረድቷቸዋል።

 

የአድዋ የጦር አውድማ እና ሦስቱ የውጊያ ቀጠናዎች

ቀዳሚው ፈጠን ብሎ ወደ አድዋው ውጊያ ቀጠና የገባው በጀኔራል አልቤርቶኒ ሥር ቀዳሚውን የኢጣሊያን ባታሊዮን መርቶ የነበረው ማጆር ዴሚኒኮ ትሩኢቶ አስቸጋሪውን የ10 ማይል ጉዞ በመጓዝ እኩለ ሌሊት ላይ ገንደብታ ገባ። የዚህ ኃይል እንቅስቃሴ በየትኛውም ደረጃ ከጀኔራል አልቤርቶኒ ሀሳብ ጋር ስለልተናበበ ሌሊቱን በጨረቃ እየገፋ ሊነጋጋ ሲል በኢትዮጵያ ጦር ካምፕ ውስጥ መሆናቸውን ብቻ ተገነዘቡ።

ኢትዮጵያዊያን በዕሩምታ ተኩስ ጀመሩ። ጠዋት 12 ሠዓት ላይ የተወሰኑ ደቂቃዎች ሲጨምሩ የአድዋው ጦርነት የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ላይ ተጀመረ። ከኢትዮጵያውያኑ 1 ሺህ የሚሆኑት የማጆር ቱሪቶ የመጀመሪያው አስካሪ ባታሊዮን 950 ሰው ብቻ ስለ ነበር ለቁጥር አለመቀራረባቸውም ወዲያኑ በቅፅበት ስለተረዱ፣ ከበባን እንደ አንድ ጥሩ ስልት ወሰዱ። ከወገኑ የራቀው የቱሪቶ ሠራዊት ከጥቅም ውጭ ሆነ። ሠፊ ርቅት በመከሰቱ ጀኔራል አልቤርቶኒ ለማጆር ቱሪቶ መድረስ ከፈለገ ብዙ ሠራዊቱን ለመስዋትነት ይዳርጋል። የኢትዮጵያውያኑ ከበባ ቱሪቶ ወደ ኋላ እንዳያፈገፍግ፣ ጄኔራል አልቤርቶኒም ወደ ፊት እንዳይገሠግሥ አስገደዳቸው።

 

በሁለት ኮረብታዎች (አምባ ምድር) በየሥፍራው የመጠቀም ስልት

የግራው ኮረብታ ጠላትን ከግራ በኩል እንዳያጠቃ የተፈጥሮ መከላከያ ሆኗል።የቀኙ ኮረብታም በቀኝ በኩል ያለው ጠላት እንዳያጠቃ ይከላከላል። ሁለቱን ኮረብታዎች ያገናኘው መሬት ኢትዮጵያውያን መድፎችን ጠምደውበታል። ከዚህ ገዥ መሬት ላይ የአልቤርቶኒ ኃይል ሲንቀሳቀስ በግልፅ ይታያል።

ስለዚህ ሠራዊት ከሠራዊት ጋር በግላጭ መሬት ላይ መዋጋት፣ በከባድ መሣሪያ ሽፋን መስጠት ሆነ። ኢትዮጵያውያኑ የፈለጉትና ያሰቡት ያ ዓይነት አሰላለፍ እንዲሆን ነበር። ሆነላቸው። ከዚህ የቅንጅትና የስልት ሕይወት ውስጥ መድፈኞች፣ባትሪዎች መቀሌ ላይ ከነበራቸው አሰላለፎች ጋር በተመሣሠለ መልኩ አድዋም ላይ ውጤታማነታቸውን አሳዩ።

የሥራ ክፍፍል ተደርጎ መድፈኞችን ማበረታታት፣ እቴጌ ጣይቱ 5 መድፎችን ሥራዬ ብለው በአስተኳሽነት በመሳተፍ ውጊያ ላይ ነበሩ። የራስ መኮንንና የራስ ሚካኤል 15 ሺህ ሠራዊት አልቤርቶኒን በቀኝ በኩል ከበቡት፣ በተመሳሳይ ሰዓት የንጉሥ ተክለኃይማኖት፣ የዋግሹም ጓንጉልና የእቴጌ ጣይቱ ኃይል አልቤርቶኒን በግራ በኩል ከበቡና የኢጣሊያን ሠራዊት በከበባ አጣብቂኝ ውስጥ በማስገባት ወቀጡት። ይህ የጦር ታክቲክ የኢትዮጵያ የረዥም ዘመን የውጊያ ስልት ስትራቴጂና ስልትን መጠቀም በትክክል የተተገበረ ነበር። ይህም ኢጣሊያኖች እንዲበታተኑ፣አቅማቸውን እንዲዳከም ያደረገ ስልትና ቅንጅት በመሆኑ የተቀረው ብዙሃኑ የኢትዮጵያ ሠራዊት ጊዜና እስትንፋስ አግኝቶ ወደ ውጊያው እምብርት ለመንቀሳቀስ ቻለ።

2ኛውጄኔራል ዳቦርሜዳ ለአልቤርቶኒ እርዳታ በመስጠት ወደ ውጊያ በቀኝ በኩል ሲገባ በማሪያም ሻዊት በኩል ወደ አድዋ ፈጥኖ ሲንቀሳቀስ ሌላው ጄኔራል አርሞንዲ ከገንደብታ በፍጥነት ዳቦርሜዳ የለቀቀውን ሥፍራ በመዝጋት ላይ እያለ ዳቦርሜዳ ራሱ አቅጣጫ በመሳት ወደ ግራ ማጥቃት ሲገባው ወደ ቀኝ ተንቀሳቀሰ። የኢትዮጵያውያን ቅንጅት እና ታክቲክ፡ ቶሎ በፍጥነት የኢጣሊያን የአሰላለፍ ምስቅልቅልነትን ተረዱ።

ጊዜ ሳይባክን ስህተቱን ተጠቀሙበት። የዳቦርሜዳ ኃይል ከአልቤርቶኒ ጋር አለመቀናጀቱ ግልፅ ሆነላቸው ማለት ነው። ዳቦርሜዳ ምንም ጥቃት እንደማያደርስ የተረዱት ኢትዮጵያውያን 15 ሺህ እግረኛ ተዋጊዎችን በማስገባት አልቤርቶኒንና ዳቦርሜዳን እንዲነጣጠሉ አደረጉ። ይህ 15 ሺህ ኃይል አደገኛ ኃይል በመሆኑ የዳቦርሜዳን በ3 ሰዓት ከ30 ደቂቃ አካባቢ ለባራቴሪ ባደረገው ሪፖርት ገልጿል። እነዚያ 15 ሺህ ወታደሮች የራስ መኮንን እና የራስ መንገሻ ሠራዊት ነበሩ። ከ3 ሰዐት 30 በኋላ ይህ የሁለትዮሽ ኃይል የኢጣሊያንን የአልቤርቶኒን ተዋጊ ኃይል ወደ ሦስት ስፍራ ተነጣጥለው ዋጋ ቢስ እንዲሆኑ አደረጋቸው። የእቴጌ ጣይቱ ሠራዊት በራስ መንገሻና በራስ መኮንን ሠራዊት የተቆራረጡትን ኃይሎች ማውደም ጀመረ።

እንደ እውነቱ ከሆነ በሁለቱም ባላንጣዎች ላይ ኃይለኛ ዕልቂትን ያሳየ የተጋጋለው የአድዋ ጦርነት ኢጣሊያኑ ከጧቱ 12 ሰዓት ተኩል ላይ የጀመሩት ማጥቃት ወደ 3 ሰዓት ከ30 ደቂቃ አካባቢ ተፍረከረኩ። መረጃዎች የሚያስቀምጡት በቅንጅት ማፍረክረክ የተባለው ኢትዮጵያዊው የዚያ ዘመን ታክቲክ ይህ ነበር።

 

3ኛ የውጊያውን ዕምብርት የማፍረስ የመጨረሻው ታክቲክና ቅንጅት

የኢትዮጵያ ሠራዊት የአልቤርቶኒንና የዳቦርሜዳን የክፍተት ስህተት ተገንዝቦ በየስፍራው ጠላትን የመምታት አቅሙን በተግባር ባዋለበት በዚያች ሰዓት በወታደራዊ ጠበብቶች እይታ የኢትዮጵያ ሠራዊት ለአገራቸው የአድዋን ድል ማስመዝገባቸው የታወቀ ጉዳይ ሆኖ ነበር። የበርሃው መብረቅ የበጋው ብራቅ የዶጋሊው አራስ ነበር ራስ አሉላ አባ ነጋ በፍጥነት ይህ አጋጣሚ ሳይቆይ እንዲተገበር ወሳኝ የጦር መሪ ሆነዋል። ይህንን ጉዳይ ሲተገብሩ ራስ አሉላ ለንጉሠ ነገሥቱ ያስተላለፉት መልክዕት በመድፍ፣በመትረየስ፣በጠመንጃ ስለወጠርናቸው በአስቸኳይ የኦሮሞ ፈረሰኞች ከራስ ሚካኤል ጦር ውስጥ በብዛትና በፍጥነት አካባቢውን እንዲያጥለቀልቁትና ከምሥራቅ አቅጣጫ መንገድ ዘግተው በጨበጣ የኢጣሊያኑ ኃይል እንዲለቅሙ ብለው ስለተመካከሩ ዉጊያዎቹ ድልን በድል ላይ ጨመሩ።

ጦርነቱ አልቋል ውጊያዎች ግን ቀኑን ሙሉ ተካሄዱ። ከጧቱ 3 ሰዓት ተኩል ጀምሮ በሌላ አቅጣጫ ወደ ወጊያው የገባው የአርሞንዲ ሠራዊት በተራው ተመታ። በሁሉም አቅጣጫ በጥልቅት የኢጣሊያን ወራሪ ኃይል በቀለበት ውስጥ በማስግባት ሙት፣ቁስለኛ፣ምርኮኛ ማድረጉን አረጋገጠ። ይህንን የመሰለ የውጊያ አቅም ተጠቅመው በጄኔራል ዳቦር ሜዳ ፣በጄኔራል አርሞንዲ፣በጄኔራል ኤሌና ተዋናይነት በኢትዮጵያ ላይ የተከፈተው የሮማ ቄሳር ጦርነት ፣የቅኝ ግዛት ዓላማው አልቤርቶኒና አድዋ የሕልም እንጀራ ሆነ። የአድዋ የድል የሕልም እንጀራ እንዲሆን አደረገው!!

 

ሥለላ እና የአድዋ ድል

በራስ አሉላ አባ ነጋ እና በራስ መንገሻ በኩል በቂ አቅም የነበራቸው እና ግሩም ስራ የሰሩ የመረጃ ሰዎች ነበሩ። በሚስጥር የተዘረጋው የመረጃ መረብ ዕርዳታና ድጋፍ የኢትዮጵያ ዘማች ሠራዊት በኢጣሊያ የጠላት ሠራዊት ላይ ከፍተኛ የሆነ ጫና እንዲያሳድር ረድቷል። በሻይ አውዓሎምና በራስ አሉላ እና በራስ መንገሻ ሥር የነበሩት ሌሎች ሰዎች የመሬትና የባህል እውቅት፣የቋንቋ ችሎታና ከኢጣሊያኑም ጋር በነበራቸው የውስጥ ለውስጥ የመረጃ ስራ ብዙ ዘዴ በማካበት የሰጡት መረጃ ኢጣሊያኑን ሠራዊት በሚጎዳና የውጊያውን አጀማመር ኢትዮጵያዉያኑን ዘማች ሠራዊት በሚጠቅም መልኩ በማድረጋቸው አስተዋፅኦቸው እጅግ የጎላ ነበር።የራስ ስብሐትና የደጃዝማች ሐጎስ ከኢጣሊያን ወገን ከድተው ወደ ኢትዮጵያ ሠራዊት መቀላቀል ብዙ መረጃዎችንም ይዞ ስለመጣ ሁኔታዎች ሁሉ ለኢጣሊያ ወራሪ ኃይል እንዳይመቻች አድርጎታል።የዘማቹ ሠራዊት ቆራጥነትና ብርታትም ሌላው ጀብዳዊ የታሪክ አንጓ ነው። ሠራዊቱ አልጋውን ለማቆም እንጂ ለመሸሽ አይፈልግም።አንዱ ወደ ፊት አንዱ ወደ ኋላ አይልም(መርስዔ ኀዘን ወልደ ቂርቆስ፡የሐያኛው ክፍለ ዘመን መባቻ) ላይ እንደ ዘገቡት። ኢትዮጵያዊ ጀግንነት ተስተውሏል፡ኢትዮጵያዊ ፅናት በእጅጉ ተንፀባርቋል ፡በመላው ዓለምም አብርቷል።

 

የአድዋ ድል ለእኛ ትውልድ የሚያስተላልፈው መልዕክት ምንድን ነው?

ኢትዮጵያ አሁን ላይ በርካታ የውጭም የውስጥም ድጋቶች ተደቅነውባታል።የምፍትሔ መንገዶችን እያማተረች ፣የቢሆን መላምቶችን እያፍታታች ባለበት ወቅት በእርግጥ የአድዋ ድል እና የዚያ ዘመን የነፃነት አርበኞች ምን መልዕክት ያስተላልፉልናል ብሎ መጠየቅ ብልህነት ይመስለኛል።እስኪ የእነርሱን አስደማሚ ጀብድ ጅማሮ እና ፍፃሜ ሰዓታት ላይ የነበሩ እልሆችን ከታሪክ ድርሳናት እንግለጥ።

ከዘመቻው ጉዞ ሂደት ጀምሮ እስከ ጦርነቱ መጨረሻ ድረስ ዝግመት፣ክፍተት፣ቅፅበትመመካከርና መከባበር በስፋት የነበሩ ክስተቶች ናቸው። በጦርነቱ ወቅት አልጋ በአልጋ የሚሆን ነገር ስለማይኖር በእነዚያ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ታልፎ የአድዋ ድል እውን ሆኗል። የእንጢጮን ተራራ በ27 ቀን በፀሐይ በሌሊት በመብራት የተገነባውን፣የተደለደለውን ትቶ እንደ ተመረዘ ጉሬዛ ከሜዳ ላይ ተዘርግፎ እንደ እህል ተወቃ። ስፍራው ቢያበጁ፣መሣሪያ ቢያደራጁ ጉልበትና ብልኃት የእግዚያብሔር መሆኑ በዚህ ተገለጠ (ፀሐፊ ገብረ ሥላሴ ገፅ257) አስፍረውታል።

ከጦርነት ድል በኋላ የተመላሹ ቁጥር ሳስቷል። ዘምተውና በውጊያው ከነበሩት ጀግኖች ውስጥ እነ ፊታውራሪ ገበየሁ ጎራው፣ደጅዝማች ጫጫ፣ደጃች ባሻህ አቦዬ፣ፊታውራሪ ተክሌ፣ቀኝ አዝማች ታፈሰና ሌሎች ያልተተቀሱት ቁጥራቸው የበዛ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች የአድዋ ጦርነት ወኪል ዋልታና ማገር በነበሩበት ብዙሃን ውስጥ ወደ ቄያቸው አልተመለሱም። የድሉን ጎዳና አፋጥነው በዚያው በእነዚያ የጥቁር ህዝቦች መመኪያ የአድዋ ተራሮች ህያው ሆነዋል። ይህ ትውልድ ከቅድመ አያቶቹ እና አባቶቹ የሰነቁለትን አስተምህሮት በተራው ለወቅታዊው ችግሮች መፍትሄ ሊጠቀምበት ይገባል።

 

ትናንት ለአድዋ ጦርነት መነሻ የሆነው የውሃ ጦርነት ዛሬም ለሌላ ጦርነት እያዘጋጀን ይሆን ?

ግብፅ እንደ እንግሊዝ ሱዳን እንደ ኢጣሊያ

ጊዜው 19ኛው ክፍለ ዘመን አይደለም።21ኛው ክፍለ ዘመን ነው።ቴክኖሎጂ መር 4ኘው የኢንዱስትሪ አብዮት የተቀጣጠለበት።ምስራቅ አፍሪካ በተለይም የአፍሪካ ቀንድ ጂኦ ፖለቲካ ደግሞ ዛሬም እንደ ትናንቱ ተፈላጊነቱ እጅግ ያሻቀበበት ወቅት ላይ እንገኛለን። ይህ ቀጣና ከግሪክ እስከ ሮማኖች፡ከኦቶማኖች እስከ ፈርኦኖች፡የቅኝ ግዛት እስከ ሁለቱ የዓለም ጦርነቶች ፡ከሁለቱ የዓለም ጦርነቶች እስከ ቀዝቃዛው ጦርነት ገፈታ ቀማሽ ሆኗል። አሁን ደግሞ በአዲሱ የእጅ አዙር ጦርነት መዳፍ ውስጥ ለመግባት በወደብ እና ጦር ሰፈር ግንባታ ከኃያላን እስከ ህዳጣን ከነዳጅ ከበርቴዎች እስከ ኒዩክሌር አረር ባለቤቶች ከፍተኛ ርኩቻ እየተካሄደበት ነው።

ውሃ ውሃ እያልን እንራመድ ! የአድዋ ጦርነት ስረ መሰረት መነሻ እንግሊዝ በኢጣሊያን በኩል የዓባይ ወንዝን የመቆጣጠር ህልም ነበር።የአድዋ ጦርነት ዋና ግብ ጣሊያን የኢትዮጵያን የተፈጥሮ ሀብት መመዝንበር በተለይም የዓባይ ወንዝን ነበር። ለፋብሪካዎቿ ጥሬ እቃ ፍለጋ እና በቀጣናው ያላትን ተስፋፋነት እና ተሰሚነት ማጎልበቻ ነበር።ያኔ ጀግኖች አርበኞቻችን የኢትዮጵያ የነፃነት ንስሮች ከሁሉም የሀገራችን ክፍል ነጋሪት ጎስመው ወደ አድዋ ተመሙ። የቄራስ ሃይላት በጥሬ እቃ ምዝበራ የታወሩ ግን ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊያን በሚገባ ያላወቁት ሰላቶዎች በአድዋ ተራሮች የኢትዮጵያን ጀግኖች ጎራዴ ፉጨት መቋቋም ተሳናቸው። የአድዋ ተራሮችም ለእነዚያ ቄሳር ሃይላት ተላላኪዎች የጎን ውጋት ሆኑባቸው። ምዕራባዊያን ለረዥም ዘመን የዘሩት የሀሰት ተረክ በአድዋ ባዶ ሆነ ፡ነጮች በጥቁሮች አይሸነፉም የሀሰት ፕሮፓጋንዳ ለፈፋ በአድዋ ባዶ ሆነ።

አፍሪካዊያን እና መላው የአለም ጥቁር ህዝቦች ብሎም በቅኝ ግዛት ቀንበር ስር የነበሩት ሌሎች ሀገራት ፓን ኢትዮጵያኒዝምን እየሰበኩ የቅኝ ግዛት ቀንበርን እስከ ወዲያኛው ጠረማመሱት ። የጣሊያን የጥሬ እቃ እና የተፈጥሮ ሀብት ምዝበራ የባህል ክለሳ በአድዋ ተደመሰሰ። የዓባይ ፖለቲካ ዛሬም ድረስ በቅኝ ግዛት ዘመን ውሎች ተሸብቦ በአዲሱ የቅኝ ግዛት እሳቤ የተሸበቡት ፈርዖኖች።ዛሬም በ1929 እና 1959 ስምምነት የመሟገቻ እና የአሳሳች ዲፕሎማሲያቸው መጋመጃ አድርገው እየባዘኑ ነው። የግብፆች ግብ እንደ ጣሊያኖች የቅኝ ግዛት መንፈስ የኢትዮጵያን የተፈጥሮ ሀብት መመዝበር ነው።

ዓባይ ለኢትዮጵያ ወንዝ ብቻ አይደለም ባህል፣ሃይማኖት ፣ እምነት፣ፍልስፍና፣ ቅኔ እና አፈር ነው። ካይሮዎች ይህን በበላይነት ያለ ማንም ከልካይነት መዝረፍ ይፈልጋሉ አርግጥ ሲሰርፉም ከርመዋል።

ሱዳን ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሲጀመር ጀምሮ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ አቋሟ ከኢትዮጵያ ጎን ነበር።ነገረ ኦማር ሀሰን አልበሽር በዳቦ አብዮት ከስልጣናቸው ሲፈነገሉ ውሃው ዲፕሎማሲም አብሮ የተቀለበሰ ይመስላል። ግብፅ እንደ ኢንግሊዝ ሱዳን እንደ ኢጣሊያ እየሆኑ መጥተዋል።

በዚያኛው ክፍለ ዘመን እንግሊዝ የዓባይን ወንዝ ሙሉ ለሙሉ በመቆጣጠር ሱዳን እና ግብፅ የሚገኙ የጥጥር እርሻ ልማቶቿን በማጎልበት ማችስተር እና ላንክሻየር ለ ሚገኙ የአልባሳት እና ጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎቿ ጥሬ እቃነት በአስተማማኝ ሁኔታ የማቅረብ ህልም ነበራት። ይህን አካሄዷን ለመግታት ሌላኛው የዚያ ዘመን ተፎካካሪ ፈረንሳይ ጂቡቲ ላይ ሆና መስፋፋት ጀመረች።የፓሪስን መንገድ በኢጣሊያ የመዝጋት የእንግሊዝ ሴራ በኢትዮጵያ እውን ሆነ ።

ኢጣሊያ ወደ ኢትዮጵያ ገባች ። ኢትዮጵያ እና ኢጣሊያ ጦርነት ውስጥ ገቡ በጦርነቱ አዳክሞ ዓባይን መቆጣጠር የእንግሊዝ ከመጋረጃው በስተጀርባ የነበረ እቅድ ነው። ዛሬ ደግሞ ግብፅ ሱዳንን ወደ ኢትዮጵያ ድንበር በመላክ ሁለቱን ሀገራት ጦር ለማማዘዝ እያሰፈሰፈች ነው። መገናኛ ብዙሃኖቻቸው 24 ሰዓታት ስለ ሁለቱ ሀገራት የድንበር ውዝግብ በርዕሰ አንቀጽነት እየዘገቡት ነው።

ሱዳንም ኢጣሊያንነቷን አጠናክራ የቀጠለች ይመስላል። ያ ኔ ኢጣሊያ የኢትዮጵያን ግዛት ወራ የእኔ ይዞታ ነው በሚል አፍራሽ አካሄድ ስትከተል ነበር። አሁን ደግሞ ሱዳን የኢትዮጵያን ግዛት ወራ እኔ ተወጋሁ እያለች የሴራ አቀነባባሪ ወኪሎቿን ከመጋረጃው በስተጀርባ ሆነው አይዞሽ የሚሏትን ወገኖች ድምፅ እና ድጋፍ ለማግኘት የአዞ እንባ እያባች ነው።

 

የሱዳን እና ኢጣሊያ ተመሳስሎ

ኢጣሊያ በ19ኛው ክፍለ ዘመን የውሃ ፖለቲካ እና የስትራቴጂክ ቅርምት አፍሪካ ቀንድ ውስጥ የገባችው ገና ሀገረ መንግስቷ የውህደት ጭቃውን ሳያደርቅ ነበር።ሱዳንም አሁን ላይ እያደረገችው ያለው እንቅስቃሴ ገና የሽግግር የፖለቲካ ትኩሳቷ እና የአልበሽር ዘመን ውልቃቶች ጥሩ ወጌሻ አግኝተው የሱዳናዊያን የምጣኔ ሀብት እድገት ጥያቄ በውል ምላሽ ሳያገኝ ነው። ያኔ እንግሊዝ ኢጣሊያንን ግፊበት እያለች የዲፕሎማሲ ሽፋን ሰጥታታለች።ዛሬም ግብፅ ሱዳንን ግፊበት እያለቻት ነው። የካይሮ ሰዎች ለካርቱም መለዮለባሸሎች በተለይም በአረቡ ዓለም የዲፕሎማሲ ድጋፍ እየሰጧቸው ነው።

የአድዋ ድል ካርድ እዚህ ላይ መሳብ አለበት።እንዴት እና በምን መንገድ የሚለው ጉዳይ ግን ገና ብዙ ተንታኞችን ፡ምሁራን እና ፖሊሲ አውጭዎችን የሚያነጋግር ቢሆንም የእኔ የምላቸውን የሃሳብ ፍንጣቂዎች በተወሰነ ደረጃ ላቅርብ ።ዋናው ጉዳይ ለውሃ ዲፕሎማሲው መፍትሄ ስትራቴጂ መንደፍ ነው። ማርክ ዜቶን እና ዬሮን ዋረን (2006 _Hydro-hegemony – a framework for analysis of trans –boundary water conflicts) በሚለው ጥናታዊ ስራቸው የውሃ የበላይነት ዲፕሎማሲን ማጠናከር የሚቻለው በሦስት ጉዳዮች ላይ ጠንክሮ በመስራት ነው።አንድም የተፋሰሱን ውሃ ሃብት በብዛት መቆጣጠር፡ሁለትም ከተፋሰሱ አባል ሀገራት ጋር የይስሙላ ትብብር እያደረጉ ታሪካዊ መብትን ማስጠበቅ ሲሰልስ ደግሞ የተፋሰሱ አባል ሀገራት እንዳይጠቀሙ የተለያዩ ዘዴዎችን ገቢር ማድረግ የሚል ነው።

ካይሮ አሁን እነዚህን ሦስት ስትራቴጂዎች ገቢር አድርጋለች ። ውሃውን በብዛት እየተጠቀመችበት ትገኛለች፡ፍትሃዊ በሚል ግን ኢፍትሃዊ አካሄድ ለማንበር ድርድር እያለች በተቃራኒው በወታደራዊ ሃይል ለማስፈራራት እየሞከረች ነው።አዲሱን የጦርነት ስልት የውክልና እና የእጅ አዙር ጮርነትም በሱዳን በኩል እየሞከረች ነው።

 

የውሃውን እሳት በውሃ የማጥፋት ድህረ አድዋ ወታደራዊ ስትራቴጂ

በዓለም ላይ ከ286 በላይ ወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ይገኛሉ። በእነዚህ ወንዞች በርካታ ሀገራት የላይኛው እና የታችኛው ተፋሰስ አባል ሆነው እየተጠቀሙባቸው ይገኛሉ። ብዙ ጊዜ በላይኛው ተፋሰስ አባል ሀገራት ግድብ እና ሌሎች የልማት ስራዎች ሲጀመሩ የታችኞች ተፋሰስ አባል ሀገራት እሮሮ እና እየዬ ዲፕሎማሲያዊ ጩኸታቸውን ያሰማሉ። ሁል ጊዜም መፍትሔ የሚሆነው ግን የተጀመረው ግድብ በድል ሲጠናቀቅ እና ውሃው መፍሰሱን ሲቀጥል ነው። ኢትዮጵያስ ?ኢትዮጵያው ከእነዚያ እንደ አንድ ናት ።

የታላቁ ህዳሴ የህዳሴ ግድብን በፍጥነት ማጠናቀቅ አዲሱን የግብፅ ቅኝ ግዛት መንፈስ ለዘለቄታው መስበር ነው። ጥቅሙም ለኢትዮጵያዊያን ብቻ አይደለም። ለሌሎች አፍሪካዊያን ወንድሞቻችን ጭምር እንጂ። ለምን?የአድዋ ድል ለመላው ጥቁር ህዝቦች እና አፍሪካዊያን ወንድሞቻችን አይቻል የሚመልሰለውን የቅኝ ግዛት ቀንበር መስበሪያ ርዕዮት ዓለም ነበር ፓን ኢትዮጵያኒዝም ወደ በኋላ ላይ ፓን አፍሪካኒዝም የተሸጋገረው።

አሁንም የህዳሴው ግድብ ከተጠናቀቀ በሁሉም የናይል ተፋሰስ አባል ሀገራት ግብፅን እንዴር ተቋቁመን እንችላለን ለሚለው የዘመን ግርጃ መቀልበሻ ጥቁር ማቅ ማውለቂያ ሞዴል ነው። ግድቡ ለአፍሪካዊያን ሌላም የምጣኔ ሀብት ሞዴል ይዞ የሚመጣ ነው!!

እስካሁን በአፍሪካ ግዙፍ ግድቦች በራስ ሀብት ያለ ማንም የውጭ እርዳታ የተገነባ የለም።’ የህዳሴው ግድብ ሲጠናቀቅ ይህን የክፍለ ዘመን ግርዶሽ የሚገልጥ ነው። የታላቁ የህዳሴ ግድብ የ21ኛው ክፍለ ዘመን የአድዋ ድል ብስራት የፓን ኢትዮጵያኒዝም ርዕዮት ዓለም ግማድ ነው!!

 

በሥላባት ማናዬ

ምንጭ: https://www.fanabc.com/ኢትዮጵያ-ኢጣሊያን-አድዋ-ላይ-እንዴት-አሸ/ 



Tuesday, September 7, 2021

ሃሳብመንግሥትነትን በዝርፊያ አጣችሁት፤ ይኼው አመል ቢያንስ ሽፍታ ሆኖ መኖርን እንኳን ሊነሳችሁ ነው!

መንግሥትነትን በዝርፊያ አጣችሁት፤ ይኼው አመል ቢያንስ ሽፍታ ሆኖ መኖርን እንኳን ሊነሳችሁ ነው!

(ስናፍቅሽ አዲስ ~ድሬቲዩብ)
ዛሬ የተሸሸጋችሁበትና ያምታታችሁት ህዝብ ትናንት ትዝ ብሏችሁ አያውቅም፡፡ በሥልጣን ዘመናችሁ ከመቀሌ ይልቅ ታይላንድ በአስረሽ ምቺው ከርማችሁ ለስካርና ለዝሙት የሚሆን ብር ሲነጥፍ ወገኔ ብላችሁ ትግራይ ገባችሁ፡፡

ክብርና ስልጣን ነበራችሁ፤ ግን ያልዘረፋችሁት ነገር የለም፡፡ ከመሬት ተነስተው ቢሊየነር ስለሆነ ጄነራሎች ንብረት መወረስ ሲነገር እንኳን “ከየት አመጡት?” ከሚለው ይልቅ “የተጋሩ ጥቃት” እያለ የሚያወራው ግልብ ደጋፊ አስክሯችሁ ሀገር አወደማችሁ፡፡

እኛ ያልተደረገንነው ምንድን ነው? ደርግን ጣልን ብላችሁ ስትገቡም ዘርፋችሁናል፤ ለውጥ ተቀብለናል ብላችሁ ስትወጡም ዘርፋችሁናል፡፡ አናሳ ሆናችሁ እኩል እንሁን እንኳን ስንል እንደ ድፍረት ቆጥራችሁ የብሔር ጥላቻን በመስበክ የተበታተነች ሀገር ለመፍጠር ደክማችኋል፡፡

መንግስት ነበራችሁ፤ ግን ሌብነትን ክብር ሰጥቶ ካልተያዘ ችግር የለውም በሚል መሪ የሚመራ መንግስት፤ ወታደር ነበራችሁ ግን ያለ እረፍት ኮንትሮባንድ በመነገድ ለሚሊዮኖች ስደትና ሞትና መፈናቀል ምክንያት የሆናችሁ ታጋዮች፡፡

ያካበታችሁትን ልባችሁ ያውቀዋል፤ የዘረፋችሁትም እንዲሁ ታውቁታላችሁ፡፡ አዲስ አበባን አይቶ የማያውቅ የአዲስ አበባ ኮንዶሚኒየም እጣ ወጣልኝ ብሎ የሚመጣባትን ዋና ከተማ ምን እንዳደረጋችኋት ልባችሁ ያውቃል፡፡

ኢትዮጵያውያን ላይ መድረቅ ይቻል ይሆናል ግን ልቦናችሁ የማይክደው ጸሐይ የሞቀውና ሀገር ያወቀው ብዙ ጉድ ነበር፤ ብዙ ግፍና መከራ ስቃይ እና ስቆቃ ከአስከፊ ዝርፊያና ሌብነታችሁ ጋር ተዳምሮ መንግስትነትን አጣችሁ፡፡

ሀገር ባንመራስ ክልል ብንመራስ ብላችሁ በገባችሁበት የመቀሌ መሰባሰብ ዘመናችሁም እንዲሁ የኢትዮጵያ እልቂት ሞትና መከራ ድግስ ደጋሾች ሆናችሁ፤ ዝርፊያውና ሌብነቱ ቀጠለ፤ እንደ አራት ኪሎው መቀሌን ለቃችሁ ዋሻ ከተታችሁ፤
ደግሞ ሽፍታና ነጻ አውጪ ነን ብላችሁ ትግል ስትጀምሩ ዳግም ሌብነት መርሃችሁ ይሆናል ብሎ የገመተ የለም፡፡ መርከብ ከመስረቅ ወደ ሊጥ ይዞ ሽሽት ይገባል ብሎ ማንስ ሊያስብ ይችላል?

የትግል ታሪካችሁ ሁለት ነባር እሴቶች ቆረጣና ዝርፊያ እንደሆነ ዳግም በታሪክ ፊት ለአዲስ ትውልድ አረጋገጣችሁ፡፡ ሀገር ዘርፋችኋል ብሎ ይጠላችሁ የነበረን ገበሬ ጎጆ ዘረፋችሁ፤ ሌባ ናችሁ ስትባሉ የሚሽኮረመሙ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችን መጋዘን ሳይቀር መዘበራችሁ፡፡

ይሄ ዝርፊያ ውድመትና ስቆቃ ምናልባትም ሀገርን አንድ አድርጎ በአንድ አላማ አሰለፈ እንጂ የትግሉን ጥንካሬ አልቀየረውም፡፡ ኢትዮጵያ እንዳትዘርፏት፣ እንዳትገድሏትና እንዳታፈርሷት በጽናት ከዳር ዳር ቆማለች፡፡

ትናንት ትጠየፉት የነበረውን የትግራይ ህዝብ ዛሬ መሸሸጊያ አድርጋችሁ ቢወልዳችሁ አምኗችሁ ወደ ከፋ ስቃይና መከራ እየገባ መሆኑ አያሳስባችሁም፡፡ እናንተ ከምትመሩት ህዝብ ይልቅ አንድ መለኪያ ውስኪ የሚበልጥባችሁ ጨካኞች ስለሆናችሁ ድል አደረገን ብላችሁ የታማኝ በየነን ቤተሰብ እንዲያ ስታሰቃዩ በአጻፋው የእኛ ቤተሰብ እንዲህ ያለ ነገር ቢገጥመውስ የሚለው አያሳስባችሁም፡፡ ንጹሃን የሚለው ቃል የፖለቲካ መነገጃችሁ እንጂ መርሃችሁ አይደለም፡፡

ለገዛ እናቱ የማያስብ እና በገዛ እናቴም ቢመጡብኝ ደስታዬ እጥፍ ነው የሚል ሀሺሻም ለገዛ ሀገሩ ያስባል ማለት ሞኝነት ነው፡፡ ግን ለሀገሩ የሚያስብ ሀገሩን የሚያድን ለሀገሩ የሚሆን መቶ ሚሊዮን ህዝብ አለ፡፡

https://news.et/2021/09/04/%e1%88%98%e1%8a%95%e1%8c%8d%e1%88%a5%e1%89%b5%e1%8a%90%e1%89%b5%e1%8a%95-%e1%89%a0%e1%8b%9d%e1%88%ad%e1%8d%8a%e1%8b%ab-%e1%8a%a0%e1%8c%a3%e1%89%bd%e1%88%81%e1%89%b5%e1%8d%a4-%e1%8b%ad%e1%8a%bc/

Friday, December 27, 2019

በሞጣ ከተማ በቤተ እምነቶች ላይ የደረሰው ጥቃት እየተወገዘ ነው

በሞጣ ከተማ በቤተ እምነቶች ላይ የደረሰው ጥቃት እየተወገዘ ነው

በአማራ ክልል በምሥራቅ ጎጃም ዞን በሞጣ ከተማ ዓርብ ታኅሳስ 10 ቀን 2012 ዓ.ም. ምሽት አንድ ሰዓት አካባቢ፣ በቤተ ክርስቲያንና በመስጊዶች ላይ የደረሰው የእሳት ቃጠሎ ጥቃት በመላ አገሪቱ እየተወገዘ ነው፡፡
የብዙ ሊቃውንት መፍለቂያው በሆነው በጥንታዊውና ታሪካዊው ሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ የእሳት ቃጠሎ ሙከራ መደረጉ፣ ከዚያ በኋላ ደግሞ መስጊዶችና ሱቆች መቃጠላቸው ይታወሳል፡፡
ድርጊቱ የሁለቱንም ሃይማኖት ተከታዮች የማይወክልና ለዘመናት በአካባቢውና በዙሪያው በፍቅር ያሳለፉትን ጊዜ የማይመጥን አሳፋሪ ድርጊት መሆኑን፣ በክርስቲያንና በሙስሊም ማኅበረሰቦች እየተወገዘ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኑ ጉልላት ላይ ጭስ በመታየቱ የአካባቢው ሙስሊሞችና ክርስቲያኖች በፍጥነት ተረባርበው የከፋ ጉዳት ሳይደርስ እሳቱን መቆጣጠር መቻሉ አስደሳች ቢሆንም፣ ስሜትን አስቀድመው ይሁን ወይም ሌላ ተልዕኮ ተቀብለው በማይታወቅ ሁኔታ መስጊዶችንና ሱቆችን ያቃጠሉና የዘረፉ በሙሉ በቁጥጥር ሥር ውለው ለሕግ እንዲቀርቡ የሁለቱም እምነት ተከታዮች እየጠየቁ ነው፡፡
ለበርካታ ዘመናት ጠንካራ ትስስር ያለው የሞጣ ሙስሊምና ክርስቲያን፣ በጊዜ አመጣሽ የውንብድና ሥራ የሚፈታ እንዳልሆነ ማሳያው ሰሞኑን በሁለቱም በኩል እየተደረገ ያለው የእርስ በርስ መደጋገፍ ዓይነተኛ ምስክር መሆኑን በርካታ የተለያዩ አካባቢ ነዋሪዎች እየተናገሩ ነው፡፡ ሙስሊሙ አብያተ ክርስቲያናትን፣ ክርስቲያኑ መስጊዶችን ላለፉት ሺሕ ዓመታት እየገነቡና እየተጋገዙ እንደኖሩት ሁሉ፣ ያለ ምንም ጣልቃ ገብነት ራሳቸውና የክልሉ መንግሥት የተቃጠሉትን እንደሚገነቡም እየተገለጸ ነው፡፡
በእምነት ተቋማት ላይ የሚደረግ ጥቃት መወገዝ እንዳለበት የሚናገሩት ነዋሪዎች ሰሞኑን በሞጣ አንድ መስጊድ ውስጥ የተያዘ አንገቱ ላይ ማተብ ያሰረ ወጣት፣ በድጋሚ ጥቃት ለማድረስ ሳይሆን ሆን ብሎ የክርስቲያኖችና የሙስሊሞች ትስስር ለማለያየት የተደረገ ሙከራ በመሆኑ መንግሥት ተጠርጣሪውን በደንብ መርምሮ ሥረ መሠረቱን ማወቅና ጠበቅ ያለ ዕርምጃ እንዲወስድ እየጠየቁ ነው፡፡ የክልሉ መንግሥት በክልሉ በሚገኙ የእምነት ተቋማት፣ የትምህርትና የንግድ ተቋማት ላይ በተደጋጋሚ የሚደርሱት ጥቃቶች ላይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት፣ የነዋሪዎችን ሰላም ለማደፍረስ በሚንቀሳቀሱ ሰርጎ ገቦች ላይ ጥብቅ ዕርምጃ እንዲወሰድ ተጠይቋል፡፡
የክልሉ መንግሥት የደኅንነት ግንባታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አገኘሁ ተሻገር፣ የክልሉ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ቦርድ ሰብሳቢ መልአከ ሰላም ኤፍሬም ሙሉዓለም፣ የክልሉ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሼክ ሰይድ አህመድ፣ የክልሉ አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ አብርሃምና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጥቃቱ የተፈጸመባቸውን ቤተ እምነቶች ጎብኝተዋል፡፡ መስጅዶቹን ለመሥራትም ቃል ገብተዋል፡፡ ‹‹ዛሬ ይኼ ነገር ባይፈጠር መልካም ነበር፡፡ ነገር ግን ተፈጥሯል፡፡ ልባችንን የሚነካ ክስተት ነው፡፡ ምናልባትም አላህ የተሻሉ ሆነው መስጅዶቻችን እንዲሠሩ ፈልጎ ይሆናል፡፡ አላህ በሰበብ አስባብ አይደል የሚያደርገው፤›› ያሉት ቀዳሚ ሙፍቲ ዑመር እንድሪስ ሲሆኑ፣ ‹‹ባለሥልጣኖቻችን ለሥልጣን ሲሉ በሕዝቡ ላይ መርዝ ነሰነሱበት እንጂ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲህ አልነበረም፤›› ብለዋል፡፡ መስጊዶች በአማራ ክልል  ብቻ ሳይሆን በተለያዩ ክልሎች የተቃጠሉ ቢሆንም፣ ድርጊቱ ግን ክርስቲያኑንና ሙስሊሙን እንደማይወክል በርካታ የሁለቱም እምነት ተከታዮች ገልጸዋል፡፡
መንግሥት ሕግ በማስከበር መስክ ከፍተኛ ድክመት እየታየበት መሆኑን የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ ጥቃት አድራሾቹን በፍጥነት በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ጠይቀዋል፡፡ ከዚህ በፊት የተፈጸሙ አሳፋሪ ድጊቶችም እንዳይደገሙ ቁጥጥሩን ያጥብቅ ብለዋል፡፡ ኃላፊነታቸውን ያልተወጡ የመንግሥት ሹሞች ተጠያቂ እንዲሆኑም አሳስበዋል፡፡
https://www.ethiopianreporter.com/article/17645

Saturday, December 21, 2019

የሰላም የኖቤል ሽልማቱ ትሩፋትና ዕዳ



የሰላም የኖቤል ሽልማቱ ትሩፋትና ዕዳ

ባለፈው ሳምንት ታላላቅ የሚባሉ ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ብዙም ባልተለመደ ሁኔታ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ከበጎ ሥራዎችና ስኬቶች ጋር በማቆራኘት፣ የዘገባቸው ማሟሻና የትንታኔያቸው ማሳያ አድርገው ሰንብተዋል፡፡
ፍረወይኒ መብራሃቱ የሲኤንኤን የዓመቱ ጀግኒት መሆኗን በመዘገብና በማብራራት ላይ እያሉ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የኖቤል የሰላም ሽልማትን መቀበል አክለውበት የመገናኛ ብዙኃኑ ስለኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ዘግበዋል፣ እየዘገቡም ነው፡፡
በተለይ ማክሰኞ ኅዳር 30 ቀን 2012 ዓ.ም. በኖርዌይ ርዕሰ ከተማ ኦስሎ ተገኝተው የሰላም የኖቤል ሽልማታቸውን በተቀበሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ፣ ከሽልማቱ ጋር በተገናኘ የተለያዩ አስተያየቶች እየተሰጡ ነው፡፡
የተለያዩ የማኅበራዊ የትስስር ገጾች ላይ ያሉ ኢትዮጵያውንም ከኖቤል የሰላም ሽልማት ሥነ ሥርዓት በኋላ ደስታቸውን ሲገልጹ፣ በተለየ መንገድ ተቃውሞ ያሰሙ ጥቂቶችም ተስተውለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሰላም ኖቤል ሽልማቱን በተቀበሉበት ወቅት ለሰላም ያላቸውን ቀናዒነት በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን፣ በተለይ ወጣት ወታደር በነበሩበት ወቅት የጦርነትን አስከፊ ገጽታ የተመለከቱ በመሆናቸው ሰላም እጅግ አስፈላጊ ነገር እንደሆነና ሁሉም ተረባርቦ ሊያረጋገጠው የሚገባ እጀግ ውድ ዋጋ ያለው ሀብት መሆኑን በአጽንኦት ሲከታተሉዋቸው ለነበሩ ሁሉ አስረድተዋል፡፡
በተለይ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት በወጣት ዕድሜያቸው በራዲዮ ኦፕሬተርነት በተሳተፉበት ወቅት በጓዶቻቸው ላይ የደረሰውን ጥቃትና ዕልቂት አስታውሰው፣ በወቅቱ የተሰው ጓዶቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ሁሌም እንደሚያስቧቸው ገልጸዋል፡፡ እንዲህ ያሉ የጦርነትን አስከፊ ገጽታ በጦርነት መሀል ሆነው መታዘባቸው፣ ለሰላም ጠንክረው እንዲሠሩ ገፊ ምክንያት እንደሆናቸውም አብራርተዋል፡፡
ከአሥራ ስምንት ወራት በፊት ወደ ሥልጣን ሲመጡ ቅድሚያ ሰጥተው ካከናወኗቸው ዓበይት ተግባራት መካከል አንዱና ዋነኛው፣ በኢትዮጵያና በኤርትራ መሀል ለ20 ዓመታት የዘለቀውን ጦርነትም ሰላምም የሌለበትን ፍጥጫ በመቅረፍ በሁለቱ አገሮች መሀል ሰላም እንዲሰፍን ማድረግ ነበር፡፡
ይህ የሰላምና የዕርቅ ውሳኔና ጥሪ ከኤርትራ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ምላሽ በማግኘቱና በሁለቱ አገሮች መካከል ተቋርጠው የነበሩት የአየር ትራንስፖርትና የቴሌኮም አገልግሎት የተጀመሩ ሲሆን፣ ለዓመታት ተዘግተው የነበሩ ድንበሮች ለጥቂት ወራትም ቢሆን ተከፍተው ነበር፡፡
ይህን በሁለቱ አገሮች ግንኙነት ላይ የተፈጠረውን ለውጥ በዋነኛነት ከግምት ያስገባው የኖቤል ሽልማት ኮሚቴም፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩን የዘንድሮ የሰላም ተሸላሚ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡
በዚህም መሠረት ሽልማታቸውን በታላቅ ሥነ ሥርዓት ተቀብለዋል፡፡ ከሽልማቱ በኋላ የተለያዩ አስተያየቶችም እየተሰጡ ነው፡፡ አብዛኞቹ አስተያየቶች አዎንታዊ ቢሆኑም፣ በኢትዮጵያና በኤርትራ መሀል ያለው ወቅታዊ ግንኙነትን በማውሳት አሉታዊ አስተያየቶች የሰጡም አሉ፡፡
በተለይ የሁለቱ አገሮች ግንኙነት አሁን ላይ በጀመረው ፍጥነት መጓዝ ባለመቻሉ፣ የድንበሮቹ መልሶ መዘጋት፣ እንዲሁም የሰላም ስምምነቱ ዝርዝር ጉዳዮች ይፋ አለመሆንና ተቋማዊ አሠራር አለመዘርጋቱን በመጥቀስ የሽልማቱ ተቺዎች የሚሰጡት አስተያየት ነው፡፡
ከዚህ በተቃራኒ ደግሞ በቅርብ ዓመታት መፍትሔ ያገኛል ተብሎ የማይገመተውን የሁለቱን አገሮች ግንኙነት በምንም ሁኔታ ቢሆን ወደ ሰላም ማምጣታቸው በራሱ ትልቅ ስኬት ነው በማለት፣ ሽልማቱና ዕውቅናው ተገቢ እንደሆነ የሚሟገቱ አሉ፡፡  
 የኖቤል የሰላም ሽልማት ኮሚቴም ቢሆን ሽልማቱን ለእሳቸው ለመስጠት ሲወስን ወቅታዊውን ሁኔታ አይገነዘብም ብሎ ማሰብ እንደሚያስቸግር የሚገልጹ ወገኖች፣ ሽልማቱ ያላቸውን ተነሳሽነትና ቀጣይ ቀጣናዊ ሁኔታዎችን ከግምት በማስገባት የተሰጠ ተገቢ ዕውቅና እንደሆነም፣ ለመከራከሪያቸው ማጠናከሪያ አድርገው ያቀርቡታል፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ በሽልማቱ ወቅት ኢትዮጵያ ቅኝ አገዛዝን ለመመከት ያሳየችው ቀደምት ተጋድሎ፣ እንዲሁም የሰው ዘር መገኛ መሆኗ ከመድረኩ መሰማቱ ሽልማቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያውን እንደሆነ በመግለጽ፣ በጉዳዩ ላይ የሚሰነዘሩ አሉታዊ አስተያየቶችን ይሞግታሉ፡፡
ከኖቤል የሰላም ሽልማት መረጣና ዕውቅና ጋር በተገናኘ የተጻፉ በርካታ መጣጥፎች እንደሚያሳዩት ከሆነ ደግሞ፣ ሽልማቱን የሚቀበሉ ተቋማትም ሆኑ ግለሰቦች የተለያዩ ተቃውሞዎችን ማስተናገዳቸው የተለመደ ነገር እንደሆነ ያወሳሉ፡፡
አንዳንድ ጽሑፎች ሽልማቱን ፖለቲካዊ አንድምታው የጎላ በመሆኑና ፖለቲካ ደግሞ የተለያየ አረዳድ፣ ትንተና፣ እንዲሁም ትርጉም የሚሰጠው ከመሆኑ አንፃር ሽልማቱ ማጨቃጨቁ አይቀሬ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡
እንደ ማሳያነትም የመጀመርያው ጥቁር አሜሪካዊ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ የሰላም ሽልማት አሸናፊ በሆኑበት ወቅት የተነሳውን ተቃውሞና ጭቅጭቅ የሚያቀርቡ በርካቶች ናቸው፡፡
ፕሬዚዳንት ኦባማ ለሰላም ኖቤል አሸናፊነት የተመረጡት ምንም ሳይሠሩና የፕሬዚዳንትነት አገልግሎታቸውም አለመፈተኑን በመጥቀስ በወቅቱ ከፍተኛ ትችት ይሰነዘሩ እንደነበሩት ሁሉ፣ ፕሬዚዳንቱ ለዓለም ሰላም በትጋት እንደሚሠሩ ቃል መግባታቸውን ተከትሎ በመላው ዓለም ከነበራቸው ተቀባይነትና የለውጥ ወኪልነት አንፃር፣ ለዓለም ሰላም ሊያበረክቱ የሚችሉትን አስተዋጽኦ ከግምት በማስገባት የተሰጣቸው ዕውቅና ተገቢ ነው በማለት የሚሞግቱ በርካቶች ነበሩ፡፡
ባለፈው ሳምንት መጀመርያ ላይ ሽልማታቸውን የተቀበሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይም፣ እንዲህ ከመሰሉ ክርክሮች ሊያመልጡ እንደማይችሉ ከዚህ ዓለም አቀፋዊ ሁኔታና ትንታኔ መረዳት ይቻላል፡፡
በዚህም ምክንያት በተለይ በርከት ያሉ ኤርትራውያን እንደ አልጄዚራና ሲኤንኤን በመሳሰሉ መደበኛ የመገናኛ ብዙኃን፣ እንዲሁም በተለያዩ የማኅበራዊ ትስስር ገጾች ላይ የኤርትራ መንግሥት በአገሪቱ ዜጎች ላይ እየደረሳቸው ያሉ በርካታ ጉዳዮች በመዘርዘር ተቃውሞ ያሰሙ ሲሆን፣ በኦስሎ ከተማ ተገኝተውም የተቃውሞ ሠልፍ አድርገዋል፡፡
ነገር ግን ለእነዚህ ግለሰቦች በርካታ ኢትዮጵያውን ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የኤርትራ የውስጥ ጉዳይ የኤርትራውያን እንጂ የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ጉዳይ አይደለም፣ ሽልማቱም የተሰጠው በሁለቱ አገሮች ለዓመታት ተቋርጦ የነበረውን ግንኙነት በማደሳቸው እንጂ፣ ኤርትራውያኑ የሚያነሱትን የዴሞክራሲና የመልካም አስተዳደራዊ ጥያቄ እንዲፈቱ በማድረጋቸው አይደለም በማለት፣ ለተቃውሞው ምላሽ በመስጠት ተጠምደው ሰንብተዋል፡፡
ሌላው በማኅበራዊ ትስስር ገጾች ከሽልማቱ በኋላ ሲሰነዘሩ የነበሩ አስተያየቶች ደግሞ ሽልማቱ ተገቢ መሆኑን የሚጠቅሱ ቢሆኑም፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሽልማቱንና የዕውቅናውን ያህል በአገሪቱ የተለያዩ ሥፍራዎች የሚስተዋለውን የሰላም ዕጦት በመቅረፍ፣ በመላ አገሪቱ መረጋጋት በማስፈን የሰላም አባትነታቸውን ማስመስከርና ማረጋገጥ እንደሚገባቸው የሚወተውቱ ናቸው፡፡
ከኢትዮጵያውያን የማኅበራዊ ትስስር ገጾች ውትወታ በተጨማሪም፣ የተለያዩ ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃንም ሽልማቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰላም ዘርፍ ተግተው እንዲሠሩ በር የሚከፍት ዕውቅና እንደሆነ ከመግለጽ ባለፈ፣ ሰላምን በመላ አገሪቱ ለማስፈንና በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ያሉ አለመረጋጋቶችን ዘላቂ መፍትሔ ከመስጠት አንፃር ከፍተኛ ሥራ የሚጠብቃቸው ከመሆኑ አንፃር ሽልማቱ አብሮ ይዞት የመጣው ዕውቅና ብቻ ሳይሆን፣ ከፍተኛ ኃላፊነት መሆኑንም በዘገባቸው አንፀባርቀዋል፡፡
የሰላም የኖቤል ሽልማት መሰጠት የጀመረው እ.ኤ.አ. ከ1901 ዓ.ም. ጀምሮ ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ 100ኛ የሰላም የኖቤል ሽልማት ተሸላሚ ናቸው፡፡ ከዚህ ቀደም ከአፍሪካ ተሸላሚዎች ተርታ ተሠልፈዋል፡፡
የኖቤል ሽልማት መርሐ ግብሮች ሰላም፣ ኢኮኖሚክስ፣ ሥነ ጽሑፍ፣ እንዲሁም የሳይንስ ዘርፎችን የሚያካትት ሲሆን፣ በእስካሁኑ የሽልማት ሥነ ሥርዓትም ለ597 ጊዜያት ያህል በተካሄዱ የሽልማት ሥነ ሥርዓቶች ለ950 ግለሰቦችና ተቋማት ሽልማቱ ተበርክቷል፡፡
ከአፍሪካ የሰላም የኖቤል ሽልማትን እ.ኤ.አ. በ1960 በመቀበል ደቡብ አፍሪካዊ መምህር፣ ወትዋችና ፖለቲከኛ የነበሩት የአፍሪካን ብሔራዊ ኮንፈረንስ (ANC) ፕሬዚዳንት የነበሩት አልበርት ሉቱሊ ቀዳሚ ሲሆኑ፣ ከእሳቸው ቀጥሎ በርካታ አፍሪካውያን ሽልማቱንና ዕውቅናውን አግኝተዋል፡፡
የኖቤል የሰላም ሽልማትን የተቀበሉ ሌሎች አፍሪካውያን ደግሞ የግብፅ ፕሬዚዳንት አንዋር ሳዳት፣ በእስራኤልና በግብፅ መካከል የነበረውን አለመግባባት ለመፍታት ላሳዩት የሰላም መነሳሳት ከእስራኤል ፕሬዚዳንት ሜናሂም ቤጊን ጋር እ.ኤ.አ. በ1978 በጋራ ሽልማቱን ተቀብለዋል፡፡
በደቡብ አፍሪካ የነበረውን የአፓርታይድ ሥርዓት ጋር ተያይዘው የተፈጠሩ አለመግባባቶችን በሰላም ለመፍታት ባደረጉት አስተዋጽኦ እንዲሁ በ1984 ዓ.ም. የኖቤል ሽልማት ለቄስ ዴዝሞንድ ቱቱ የተበረከተ ሲሆን፣ ሌላው ደቡብ አፍሪካዊ የነፃነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ በ1993 ዓ.ም. ከፌሬደሪክ ዴክለርክ ጋር ሽልማቱን ወስደዋል፡፡
ከእነዚህ በተጨማሪም ጋናዊው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ የነበሩት ኮፊ አናን በ2001 ዓ.ም.፣ ኬንያዊቷ የአካባቢ ጥበቃ ተቆርቋሪ ዋነጋራ ማታይ በ2004 ዓ.ም.፣ ግብፃዊው የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ዳይሬክተር የነበሩት መሐመድ አልባራዳይ በ2005 ዓ.ም.፣ የቀድሞ የላይቤሪያ ፕሬዚዳንት የነበሩት ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍ በ2011 ዓ.ም.፣ እንዲሁም የፀደይ አብዮትን ተከትሎ በቱኒዝያ ተፈጥሮ የነበረውን አለመረጋጋት ለመፍታት አስተዋጽኦ ላበረከቱት የቱኒዝያ ናሽናል ዲያሎግ ኳርቴት እንደ ተቋም ሽልማቱን በመውሰድ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይም እዚህን አፍሪካውንን የሰላም ሽልማቱን በመቀበል የተቀላቀሉ ሲሆን፣ በአገሪቱ ሰላም ለማስፈን ከፍተኛ ጥረት ከፊታቸው እንደሚጠብቃቸው የሚገልጹ በርካቶች ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር የሽልማቱን በረከት ወደ ተጨባጭ ተግባር ለመቀየር እንደ መነሻ እንደሚሆንና ያላቸውን የሰላም ቀናዒነት ማረጋገጫ ማኅተም ተደርጎ ይወስድ ዘንድ፣ በመላ አገሪቱ ሰላምን ማስፈን ከፊታቸው እንደሚጠብቃቸው በርካቶች ያስረዳሉ፡፡
https://www.ethiopianreporter.com/article/17572